Thursday, July 21, 2016

ማርያም ውቕሮ

ከአለት ተፈልፍለው ስለተሠሩ ውቅር ሕንፃዎች ሲነሳ ቀድመው የሚጠቀሱት የላሊበላ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት ናቸው፡፡ በ12ኛውና በ13ኛው ምታመት በንጉሡ ቅዱስ ላሊበላ ዘመንና ከርሱም በኋላ የታነፁት እነዚህ ውቅር ሕንፃዎች በዩኔስኮ በዓለም ቅርስነት የተመዘገቡ ናቸው፡፡ የእነዚህን ውቅር አብያተ ክርስቲያናት የግንባታ ውርስ ከዘመነ አክሱም ትውፊት የቀጠለ እንደሆነ የሚመለከት ቢሆንም፣ በአንዳንዶች በኩል በውጭ ሰዎች እንደታነፁ የሚያመለክቱ አልታጡም፡፡ ሁለተኛውን አተያይ ተቀባይነት እንደሌለው ከሚጠቅሱትና ከዘመነ አክሱም የቀጠለ እንደሆነ አመላካቹ ከላሊበላዎቹ ውቅሮች 800 ዓመታት አስቀድሞ በትግራይና በዋግ ውስጥ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት መገንባታቸው እንደሆነ ይወሳል፡፡
ከሃምሳ ዓመት በፊት በአዲስ አበባ (በሚያዝያ ወር 1958 ዓ.ም.) በተደረገው ሦስተኛው የኢትዮጵያ ባህልና ጥበብ ዓለም አቀፍ ጉባኤ ‹‹በትግራይ ጠቅላይ ግዛት ስለሚገኙ በውቅር የታሠሩ አብያተ ክርስቲያናት›› በሚል ርእስ ጥናት ከነ ልዩ ልዩ ማስረጃዎች ጋር ያቀረቡት ዶ/ር አባ ተወልደመድኅን ዮሴፍ (1908-1959) በተለያዩ የትግራይ አውራጃዎች 120 የውቅር ሕንፃዎች እንደሚገኙ ገልጸው ነበር፡፡
በጽሑፎቻቸውም እንደሚታየው በትግራይ የሚገኙትን ኢትዮጵያን የሚያኮሯትን የታሪክ የጥበብና የሃይማኖትም ቅርሶች በመግለጻቸው ቀድሞ አስደናቂዎች በሆኑ በላሊበላ ሕንፃዎች የበለጸገውን የአገሪቱን የሥነ ጥበብና የሃይማኖት ታሪክ በበለጠ እንደሚበለጽግ አድርገዋል፡፡
ከእነዚህ 120 ውቅር ሕንፃዎች መካከል አንዷ የሆነችው ማርያም ውቅሮ ቤተ ክርስቲያን ከ50 ዓመት በፊት እንደምትታወቀውና በዶ/ር አባ ተወልደ መድኅን እንደተመዘገበው፣ በዓድዋ አውራጃ በእምባሰነይቲ ወረዳ፣ በአሁኑ አከላለል በማዕከላዊ ዞን በወርዒለኸ ወረዳ በእምባሰነይቲ ንኡስ ወረዳ የምትገኘው እንዳማርያም ውቕሮ ቤተ ክርስቲያን በአራተኛው ምታመት (357 ዓ.ም.) በወንድማማቾቹ ነገሥታት አብርሃ ወአድብሃ መመሥረቷ ይነገራል፡፡
የማርያም ውቕሮ ሕንፃ ሲገለጽ
ከማዕከላዊ ዞን መቀመጫ ከአክሱም ከተማ 112 ኪሎ ሜትር፣ ከሐውዜን 34 ኪሎ ሜትር፣ ከመቐለ 125 ኪሎ ሜትር ርቀት ላይ የምትገኘው ማርያም ውቕሮ ቤተ ክርስቲያን ከውቅሩ ሕንፃ ጀርባ ለጥ ያለ ሜዳ በመሆኑ በዚያው መስመር የሚመጣ መንገደኛ ወደ ገደል እንዳይወድቅ ከመሥጋት ባለፈ፣ ቤተ ክርስቲያን መኖሩን የሚያሳይ ነገር የለም፡፡ ከሰባት ኪሎ ሜትር ርቀት ከነበለት በሰሜን ምሥራቅ አቅጣጫ በፊት ለፊት የሚመጣም አሻግሮ ቢያይም ሕንፃ ቤተ ክርስቲያኑን እንዳይመለከት በዙሪያው ያሉ ኮረብታዎች ይሸፍኑታል፡፡ ከገደላማው ኮረብታ ቀረብ የሚል ተጓዥ ከጠባቦቹ የመግቢያ በሮች ይልቅ ጎልተው የሚታዩት በውቅሩ ከፍታ መስኮት መስሎቹ ሽንቁሮች በውስጡ ቤተ ክርስቲያን እንዳለ ያመለክቱታሉ፡፡
የውቅር ሕንፃው ጠቅላላ ስፋት 20.6 ሜትር በ10.3 ሜትር ሆኖ ከፍታው (ቁመቱ) 6.9 ሜትር ነው፡፡
እንደ አስረጂው መልአከ ሰላም ዓምደብርሃን ገብረፃድቅ አገላለጽ፣ የቤተ ክርስቲያኑ አሠራር ካንድ ቋጥኝ ኮረብታ (ተራራ አከል) ተፈልፍሎ አንድ ወጥ በሆነ ውቅር ድንጋይ የታነፀ፣ ‹‹ዓመደ ጭዳ›› የሚሉት ባለአርባ አራት ምሰሶ ሆኖ በየምሰሶው ማዕዘን ጫፍንና ጠርዝ በተለያየ መልክ የተቀረፁ ሐረጎች፣ የመስቀል የማኅተምና በብዙ ኅብረ ጥበብ የተዋቡ ቅርፆች አሉበት፡፡ በየሕንፃው ግድግዳም የሥነ ሕንፃ ጌጣጌጥና ቅርፃ ቅርፅ ያሉበት ዕፁብ ድንቅ ሕንፃ ነው፡፡ በነባር ስሙ መቅደስ፣ ቅድስትና ቅኔ ማሕሌት ያለው ሲሆን በቅኔ ማሕሌቱ ከራሱ በተያያዘ ከሕንፃው በቅርፅ ተፈልፍሎ የወጣ በአንድ አካል ልክ የተቀረጸ ልዩ መልክና ውበት ያለው ቅርፅ ይታያል፡፡ የደብሩ አለቃ ወይም የአስተዳዳሪ መቆሚያም ማረፊያም ነው፡፡
ከቅኔ ማሕሌት በስተሰሜን በኩል ‹‹ምቅዋም ንግሥት ማርያም›› የሚሉት ሕንፃ አለ፤ የሴቶች መቆሚያና መፀለያ ነው፡፡ በዚያውም ወደ ቅድስት መግቢያ በር አለው፤ መንበረ ታቦቱ ሦስት ሆኖ የቅድስት ማርያም የቅዱስ ሚካኤልና የቅዱስ ገብርኤል ሲሆን ሁሉም በቅርፅ ተፈልፍለው የወጡ ናቸው፡፡
የቅድስት ማርያም መንበር ከላይ ከመንበሩ መጠን ቀስተ ደመና የሚመስል ቅርፅ አለው፡፡ የቤተ ክርስቲያኑ መግቢያዎች ሦስት በውስጥ ሦስት በውጭ ስድስት ሲሆኑ ባለሁለት ደረጃዎች ናቸው፡፡ የእነዚህ መዝጊያዎች አበው እንደሚናገሩት ከእምባጮ ዕፅ የተሠሩና እስካሁን ድረስ በአገልግሎታቸው ጉድለት የሌለባቸው ጥንካሬያቸው እንደተጠበቀ ይታያል፡፡ መወርመሪያውና መሸጎጫውም አብሮ ካንድ እንጨት የተሠራ ነው፡፡
ከቅኔ ማሕሌቱ በላይ እንደፎቅ ሆኖ የቅዱስ ጊዮርጊስ ቤተመቅደስ (ቤተ ጊዮርጊስ) ይገኛል፡፡ በትግራይ ከሚገኙት ውቕር አብያተ ክርስቲያናት አንዱ የሚለየው ባለፎቅነቱ ነው፡፡ ወደፎቁ ለመውጣት አዳጋች በመሆኑ ‹‹ነፍስህን ለፈጣሪ ሰጥተህ ነው በመሰላል የምትወጣው›› ይላሉ፡፡ ከቅድስቱ ውስጥ በስተሰሜን የመድኃኔዓለም ቤተ መቅደስ የሚሉት የነበረ ቢሆንም በአሁኑ ጊዜ የንዋየ ቅዱሳቱ ማከማቻ ቤተ መዛግብት አድርገውት ይታያል፡፡ ቤተልሔሙም እንደ ቤተ ክርስቲያኑ ሁሉ ውቅር ሕንፃ ነው፡፡
ሌላው አስደናቂ ምስጢርና ሁልጊዜም እንደተአምር እየተቆጠረ የሚነገርለት በቅድስቱ ሕንፃ ወለል በግራ በኩል ባለመዝጊያ የሆነ ረዥም የጉድጓድ ዋሻ አለ፡፡ በውስጡ የሚገኝ የምንጭ ውኃ ጥልቅ በመሆኑ በረዥም ገመድ ወይም መጫኛ አድርገው እየቀዱ ለቅዳሴና ለጠበል ይጠቀሙበታል፡፡ ዋሻው ሰፊ ሆኖ በምንጩ ውኃ ዳር የእግር መንገድ አለው ይባላል፡፡ የዕድሜ ባለጸጎች የሆኑት የደብሩ ካህናት የባትሪ ወይም የፓውዛ መብራት ተይዞ በዋሻው ብዙ መንገድ የሚያስኬድ ርቀት እንዳለው ይናገራሉ፡፡
ቤተ ክርስቲያኗ ከሌሎች ውቅር ሕንፃዎች ሁሉ የበለጠችና ልዩ የሚያደርጋት የቤተ ክርስቲያኑ ሕንፃ የታነፀበት መሣሪያ ‹‹እብነ አድማስ›› የሚባል የሰው እጅ በማይደርስበት የቤተ ክርስቲያኑ ሕንፃ ጣሪያ ላይ በብረት ሰንሰለት ተንጠልጥሎ መገኘቱና መታየቱ ነው፡፡ በዚያ ላይም ‹‹በዕብራይስጥ›› ቋንቋ የተጻፈ ጽሑፍ በቅርጹ ላይ ይገኛል፡፡
አለቱን እያቀለጡ ሕንፃውን የገነቡበት እብነ አድማስ ላይ የተጻፈው ጽሑፍ አለመተርጎሙና አለመጠናቱ የደብሩ አገልጋይ ቄስ ዘማርያም ተክለ ሃይማኖት ያወጋሉ፡፡ ከሦስቱ እብነ አድማሶች አንዱ በፋሺስት ኢጣሊያ ወረራ ጊዜ መነቀሱም ይወሳል፡፡
ይሁንና ይህን አስደናቂ የሆነውን የእምባሰነይቲ ውቅሮ ቅድስት ማርያም ሕንፃ ቤተ ክርስቲያን አናጺው ማነው? የሚል ጥያቄ በሚነሳበት ጊዜ በአካባቢው ሲነገር የኖረ የተለያየ አፈ ታሪክ ቢኖርም በጽሑፍ የተደገፈ ታሪክ እንደሚያስረዳው ከክርስቶስ ልደት በኋላ በ4ኛው ምታመት ነገሥታቱ አብርሃና አጽብሐ እንደአነጿት ያረጋግጣል፡፡ ከአብርሃና አጽብሐ ገድል የተገኘው የተመረጡ ነገሥት አብርሃ ወአጽብሐ ለዚያ ደብር (ተራራ) ሌላ መቅደስ (ቤተ ክርስቲያን) አነጹ፤ ይህችውም ኦር ለተባለው ወንዝ አቅራቢያ ናት›› ሲል ያስረዳል፡፡ ኦር ማለት በአገሬው ሕዝብ ቋንቋ ወርዒ ማለት ሲሆን በአሁኑ ጊዜ ደግሞ ወርዒ ለኸ እየተባለ የሚጠራው ነው፡፡
ቱሪስቶችን የምትናፈቀው ማርያም ውቕሮ
ከ1600 ዓመታት በላይ ዕድሜ ያስቆጠረችው የማርየም ውቕሮ ሕንፃ ምዕመናኑ በተጨማሪ ቱሪስቶችን ይናፈቃል፡፡ እንደ አካባቢው ኅብረተሰብም ሆነ ደርሶ ተመላሹ አገላለጽም በአስደናቂ ሕንፃነቱ ለዓለም ቅርስነት ለመመዝገብ አቅም ያለው ቢሆንም በመሠረተ ልማት በተለይም በመንገድ ችግር ምክንያት ለዓለም ሕዝብ ቀርቶ ለአገር ቤትም ብዙ ሳይታወቅ ቆይቷል፡፡
እንደ መልአከ ሰላም ዓምደ ብርሃን ገብረፃድቅ መግለጫ፣ በሁለት አቅጣጫ በሐውዜንና በዓድዋ ዕዳጋ ዓርቢ በኩል እስከ ነበለት ከተማ ድረስ የነበረው የመንገድ ችግር የተቃለለ ቢሆንም፣ ከነበለት ከተማ እስከ ማርያም ውቕሮ ሕንፃ ድረስ ያለው መንገድ ግን በምስማዕ ወንዝ ድልድይ አለመሠራት ምክንያት ችግሩ አሁንም እንዳለ ነው፡፡ በጋ ሲሆን ብቻ አንዳንድ ጠንከር ያሉ ተሽከርካሪዎች በብዙ ጥንቃቄ እስከ ቤተ ክርስቲያኑ ድረስ ይደርሳሉ፡፡
ሰኔ 21 ቀን 2008 ዓ.ም. በተከበረው ሕንፀተ ቤተ ክርስቲያን በዓል የተገኙት ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ ቀዳማዊ ይኸንኑ የመንገድ ችግር አንስተው በተለይ መንግሥት ትኩረት እንዲሰጥበት ጥሪ አቅርበዋል፡፡
‹‹የዚህ ታሪካዊ ቦታ ሃይማኖታዊ ቅርስን በማስጠበቅ አካባቢውን በማጽዳትና በማልማት የተጀመረው ልማት ቀጥሎ፣ የአካባቢው ተወላጆችና ምዕመናን እንዲሁም የቅርሱ ተቆርቋሪዎች በመተባበር መንገዱንና ድልድዩን አሠርታችሁ ለቱሪስቶች መስሕብነት የተመቻቸ ማድረግ ይጠበቅባችኋል፤›› ብለዋል፡፡
‹‹ፍጡነ ረድኤት››
ከሺሕ ዓመታት በላይ ዕድሜ ያስቆጠረው ውቅር ሕንፃ በዘመን እርጅና ሳቢያ አካባቢው ምቹነት አጥቶ ለምዕመናኑም ሆነ ለካህናቱ፣ ለአካባቢው ኅብረተሰብ አዳጋች ሆኖ ዘመንን ቆጠረ፡፡ ለመሳለምም ሆነ ለመጎብኘት የሚደርሰውም ቁጥር አነስተኛ ሆነ፡፡ በአጥቢያው የንግሥ በዓል ኅዳር እና ሰኔ በ21ኛው ቀን ከማይለዩ በቀር፡፡
መልአከ ሰላም ዓምደ ብርሃን በድርሳናቸው እንደገለጹት፣ የቤተ ክርስቲያኑ ቅፅረ ግቢ አፈሩ እየተሸረሸረ አልቆ፣ ወደ ቤተ ክርስቲያኑ ለመግባትና ለመውጣት በተለይ ሌሊት በጨለማ ጊዜ እያንሸራተተ እጅግ ያስቸግር ነበር፡፡ ይህንን የተገነዘቡት የአካባቢው ተወላጅና በዲቁና ያገለገሉት በጎ አድራጊው አቶ ብርሃነ ግደይ ከባለቤታቸው ወ/ሮ ዓለም አረጋዊ ጋር በመሆን ከአራት ሚሊዮን ብር በላይ በሆነ ወጪ ለደብሩ የሚጠቅሙ የልማት ሥራዎችን ሠርተዋል፡፡ ለዕርዳታ ፈጥነው ደርሰዋል፡፡ ፍጡነ ረድኤት ሆነዋል፡፡ ወደ ቤተ ክርስቲያኑ መዳረሻ የሚወስደውን ወጣ ገባ አስቸጋሪ መንገድ ለማስተካከል ሰፊ ዓውደ ምሕረት እንዲሆን በአራት ዕርከን ደልድለው ምቹ አገልግሎት እንዲሰጥ በማድረግ እንዲሁም ለእንግዶች (ጎብኚዎች) ማረፊያና መጠለያ አዳራሽና አምስት የመኝታ ክፍሎችና የንጽሕና ክፍሎች ማሠራታቸው በምረቃው ወቅት ተወስቷል፡፡
የመሠረተ ልማት ሥራዎቹን ቅዱስ ፓትርያርኩ አቡነ ማትያስ የመረቁ ሲሆን በሥነ በዓሉ ላይ እንደተናገሩትም ‹‹የቀደሙት አባቶቻችን እግዚአብሔር በገለጸላቸው ጥበብ ይህን አስደናቂ ሕንፃ ሠርተው ማስተላለፋቸውን ታሪክ ሲያስታውሳቸው እንዲኖር ሁሉ፣ እንደዚሁም በጎ አድራጊው አቶ ብርሃነ ግደይ በዚህ ታሪካዊ የቅርስና የሃይማኖት ቦታ በሠሩት በጎ ሥራ ሁሉ ታሪክ ለዘላለም እንደሚያስታውሳቸው እሙን ነው፡፡››
የ51 ዓመቱ ድምፅ!
በልዑል ራስ መንገሻ ሥዩም አሳሳቢነት፣ በውቅር ስለተሠሩት የትግራይ አብያተ ክርስቲያናት ሕንፃዎች ለመጀመሪያ ጊዜ በ1958 ዓ.ም. በይፋ በዓለም አቀፍ ጉባኤ በሰነዶች በታጀበ ማስረጃ ያስተዋወቁት፣ ነፍስ ኄር ዶ/ር አባ ተወልደመድኅን ዮሴፍ ለፈጸሙት አኩሪ ተግባር በወቅቱ ቀዳማዊ ኃይለሥላሴ ላንድሮቨርና ዘመናዊ የሥዕል ማንሻ (ካሜራ) ከወርቅ ሜዳሊያ ጋር ሸልመዋቸው ነበር፡፡ ከጉባኤው አንድ ዓመት በፊት ኅዳር 7 ቀን 1957 ዓ.ም. በአዲስ ዘመን ያሰሙት ድምፅ አሁንም ገደል ማሚቶ ሆኖ ያስተጋባል፡፡ እንዲህ ሲሉ ጽሑፋቸውን ጀመሩ፡፡
‹‹አንድ የውጭ አገር ሰው ሊቅ በቅርብ ዓመታት በአማርኛ ታትሞ በወጣ የኢትዮጵያ ታሪክ መጻፉ ውስጥ፤ ስለ ላሊበላ ሕንፃዎች ብቻ ሲናገር እንዲህ ይላል፤›› ሲሉም ቀጠሉ፡፡ ‹‹የኢትዮጵያን ታሪክ የሚመረምሩ ሁሉ፤ እስካሁን ድረስ የላሊበላ አብያተ ክርስቲያንናት የተፈለፈሉበትን የጥበብ ምሥጢር አላገኙትም፡፡ እንደዚህም ማለት በዓለም ላይ ብቻውን የሚገኘውን እንደዚህ ልዩ የሆነውን ሥራ በምን ዓይነት መሥራት እንደቻሉ አላወቁትም ማለት ነው››፡፡ አያይዘውም ሠለሱ፡፡ ‹‹በተጠቀሰው የታሪክ ጸሐፊ ሐሳብ ላይ እርሱን በመከተል ይህንንም ማሰብ እንችላለን፤ ማለት ለግብጽ የፒራሚድ ሐውልቶች ትልቅ መታሰቢያና መለዮ እንደሆኑ ለኢትዮጵያም የአክሱም ሐውልቶችና ከመቶ የሚበልጡ የላሊበላና የሰቆጣ፤ የትግራይ ሕንፃ ውቅር አብያተ ክርስቲያናት አስደናቂዎች መታሰቢያዎችና መለዮዎች እንደሆኑ አሳምረን መገንዘብ አለብን፡፡ ስለዚህም ከሁሉም የዓለም አህጉሮች ኢትዮጵያ አገራችን ብቻ ግምት የሌለው ታሪካዊ ሀብት፣ ማለት ከመቶ በላይ የሆኑ በውቅር የታነፁ አስደናቂዎች አብያተ ክርስቲያናት እንደሚገኙባት ማወቅ፤ ለኢትዮጵያን ሁላችን ወሰን የሌለው ደስታ ሊሰማን ይገባል፡፡
‹‹ተራራዎች እየፈለፈለች፤ በትልቅ ጥበብና ትጋት አለቶችን እየወቀረች የማይፈነቀል የክርስትና ትልቅ እምነቷን በጠንካራው አለትና በተራራዎች ሆድ ውስጥ የመሠረተች ታላቋ ኢትዮጵያ አገራችን፣ በሌሎች የዓለም አህጉሮች የማይገኙ፤ በብዛታቸውና በአስተናነጻቸውም የሚያስደንቁ በውቅር የታነፁ አብያተ ክርስቲያኖቿ በእውነቱ ልትኮራባቸውና ልትደሰትባቸውም የሚገባት ናት፡፡ ዳሩ ግን በዚሁ ምክንያት ለእነኚህ ለምትኮራባቸው ሐውልቶችና በውቅር ለተሠሩ አብያተ ክርስቲያኖቿ ባስፈላጊ ዘዴና ጥንቃቄ ልትይዛቸው ከማርጀትና ከመበላሸትም ልትጠብቃቸው ይገባታል፡፡ እንዲሁም ተገቢ በሆነ ዝግጅት በውቅር ስለ ተሠሩ አብያተ ክርስቲያኖቿ የታተሙ ጽሑፎችን እየዘረጋች በሞላው ዓለም እንዲታወቁ ማድረግ፣ የተባሉት ሐውልቶቿና አብያተ ክርስቲያኖቿ በደንብ ተጠብቀው ለመጪዎች ትውልዶች ማስተላለፍ ኢትዮጵያ ከፍ ያለ ኃላፊነትና የተቀደሰ ተግባር እንዳለባት ልትዘነጋው አይገባትም፡፡››

ማርያም ውቕሮ - ከዓለም የተደበቀው የ1600 ዓመቱ ቅርስ

 የእመቤታችን የቅድስት ድንግል ማርያምና የአርባ ሓራ መድኃኒዓለም ተዐምር


No comments:

Post a Comment